Sunday, March 15, 2015

የምርጫ ክርክር አንድ፡ መድበለ ፓርቲ ሰርዓት እና ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብት- በእኔ ዕይታ


ተከራካሪ  “ፓርቲዎች”
ኢህአዴግ፤   አቶ አሰመላሽ ገ/ስላሴ እና አቶ ሬድዋን ሁሴን (ዋና ተከራካሪ ማን እንደሆነ ባይነገርም ይታወቃል)
አትፓ፤      አቶ አሰፋው ጌታቸው
መድረክ፤    ዶር መረራ ጉዲና
ሰማያዊ፤    አቶ ይልቃል ጌትነት እና አቶ ዮናታን ተሰፋዬ
“አንድነት”፤  አቶ ትዕግሰቱ አወሉ
ከዚህ በታች የማቀርበው አስተያየት የግል ምልከታዬን ሲሆን፤ ሰዎች በተለያየ አረዳድ ሊኖራቸው እንደሚችል መታወቅ ይኖርበታል፡፡ በዘንድሮ ክርክር አንድ ጥሩ ነገር የውይይት ቅደም ተከተል በተራ እንዲሆን መደረጉ ሲሆን ይህ ኢህአዴግ የተሳሳተ መረጃና መደምደሚያ ሰጥቶ አድማጭ እንዳያደናገር ቢያንስ እድል ፊቷን አዙራበታለች፡፡ የመጨረሻውን መልካም እድል ያገኘው “የድንኩ አንድነት” ተወካይ አቶ ትዕግሰቱ አወሉ ቢሆንም በሙሉ ልብ የሚያከራክር ልዕልና ባለመያዙ ይህን ዕድል አልተጠቀመበትም፡፡ ሁለም ፓርቲዎች ከዋና ተከራካሪ በተጨማሪ አንድ አማካሪ ይዘው የገቡ ሲሆን ከሰማያዊ ፓርቲ በስተቀር ሌሎቹ ዕድል ሳያገኙ ወጥተዋል፡፡ ምክር ስለመስጠታቸውም ተመልካቾች እርግጠኞች አይደለም፡፡ አቶ ትዕግሰቱ አወሉ ይዞት የመጣው ግለሰብ ግን ሊመክረው እንደማይችል እርግጠኛ ነኝ፡፡ አንድነትን ድንክ በማድረግ ለዋለው ውለታ በቴሌቪዥን እንዲታይ ብቻ ይመሰለኛል፡፡ የዚህን ያህል እንደ መግቢያ ካልኩ ይበቃኛል፡፡
ኢህአዴግ ለ2007 ምርጫ ክርክር አዲስ ሀሳብ ሆነ አዲስ ሰው እንደሌለው ያረጋገጠበት መድረክ ነበር፡፡ ኢህአዴግ አብዮታዊ ወይም ልማታዊ ዲሞክራሲ እያለ በተለያየ ስም የሚጠራውን መስመር (ርዕዮተዓለም ሊባል ስለማይቻል) የሚያስረዱለት ዋነኛውን ሰው አቶ አስመላሽ ገብረስላሴን፤ እንደ አሰፈላጊነቱ ያለምንም ይሉኝታ ሊሳደቡ የሚችሉትን የስድብ አባት የሆኑትን አቶ ሬድዋን ሁሴንን ይዞ በክርክር መድረኩ ላይ ተሰይሞዋል፡፡ ኢህአዴግ የተሰጠውን የመጀመሪያ 15 ደቂቃ አሁንም ደርግን በጣለበት ጀግንነት ሰሜት ውስጥ ሆኖ አውቀው ይሆን ሳያውቁ 24 ዓመትን እንደ 24 ስዓት እንድንቆጥር እያደረጉ (በዕለቱ 24 ዓመት ለማለት 24 ሰዓት ይሉ ነበር፡፡) የለመድነውን በመንግሰትነት የሰሩትን ሰራ በፍፁም ከተቃዋሚዎች ጋር ሊወዳደሩበት የማይገባቸውን ተግባር እያነሱ ሲጥሉ ጨርሰውታል፡፡ ለተቃዋሚዎች ምንም እውቅና ለመስጠት ሳይዘጋጁ እውቅና በመሻት ሰሜት ውስጥ ሆነው ኦሮጌ የሆነውን የመነሻ ሀሳባቸውን አቅርበዋል፡፡ የ2002 ክርክር በድጋሚ ቢቀርብ ለውጡ አቶ አሰመላሽ የተኳቸው ተከራካሪ ያለመኖር ብቻ ነው፡፡
ቀጣዩን መድረክ በቅድሚያ የተረከበው አዲስ ትውልድ ፓርቲ በመባል የሚታወቀው የአቶ አስፋው ጌታቸው የግል ፓርቲ ነው፡፡ የግላቸው መሆኑን መጠራጠር አያስፈልግም፡፡ የቅስቀሳ ፅሁፍ ከማንበብ ጀምሮ በማንኛውም ስብሰባ ላይ ብቸኛው ተወካይ የሆኑት እኚህ ሰው በእርግጥ ሰማቸው እንደሚለው ይህን ትውልድ አይወክሉም እንጂ፤በመጀመሪያው ዙር ለትውልድ ማፈሪያ በሚሆን ደረጃ ለክርክር ቀርበው አግኝተናቸዋል፡፡ እንደ ዕድል ሆኖ ከተቃዋሚ ተብዬዎቹ የመጀመሪያ በመሆናቸው ደግሞ በቀጣይ ለሚከራከሩት ሰዎች ማፈሪያ በሚሆን አጀማመር የጀመሩትን ከፍ ለማድረግ አስቸጋሪ ሁኔታ እንደፈጠሩባቸው መረዳት ቀላል ነበር፡፡ በግልፅ ለታዘበ አቶ ይልቃል ጌትነት ከጎናቸው ሆነው ሲሸማቀቁ ላየ ሰው የአቶ አስፋው ጌታቸው የመከራከሪያ ነጥብም ሆነ መንገድ በሌሎች ተከራካሪዎች ላይ ጉዳት አላደረሰም ሊባል አይችልም፡፡ ከጎን ላሉት አይደለም ቤታችን ለተቀመጥን ለእኛም ማፈሪያ የነበረ ክርክር አጀማመር ነው፡፡
አቶ አስፋው ጌታቸው ለክርክር ስለተመረጠው አጀንዳ “የመድበለ ፓርቲ ስርዓትና ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች” ጉዳይ አንድ ቃል ሳይተነፍሱ ስለ አረንጓዴ ቀለም ትርጉም ከረባታቸውን እና በኪሳቸው የሸጎጡትን ብጣሽ ጨርቅ እያሳዩ የተሰጣቸውን ውድ ጊዜ አጠናቀውታል፡፡ ከአረንጓዴ ትንታኔ በተጨማሪ የነገሩን ነገር ቢኖር ከኢህአዴግ ጋር ግብ ግብ ለመግጠም እንደማይፈልጉ ምለው መገዘታቸው ብቻ ነው፡፡ በእኔ እምነት አቶ አስፋው ጌታቸውም ሆኑ ፓርቲያቸው እንደ ሰማቸው ይህን ትውልድ ሊወክሉ አይችሉም፡፡ አቶ አስፋው ጌታቸው በዚህ ውድ ጊዜ ውስጥ ስለ ግል የትምህርት ዝግጅትና ግላዊ ጉዳይ ለማውራት የወሰዱት ጊዜ በኢትዮጵያ ስለ አለው አስከፊ የሰብዓዊ መብታ ሁኔታ ለመናገር ድፍረት ማጣታቸው አሳዝኖኛል፡፡ ይህን አዲስ ትውልድ እወክላለሁ የሚል ፓርቲ የዞን ዘጠኝ በመባል እስር ቤት ያሉት ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች እንዲሁም እነ ሀብታሙ አያሌው እና ሌሎች ትንታግ የዚህ ትውልድ ወኪሎች ማንሳት ነበረበት፡፡ ይህ ትውልድ ወኪል አጥቶ ሳይሆን ሁነኛ ወካዮቹ ቤታቸው በገዢው ፓርቲ ውሳኔ ወህኒ መሆኑ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይህ ትውልድ በምንም ሁኔታ በአዲስ ትውልድ ፓርቲ እና በአቶ አስፋው ጌታቸው አይወከልም፡፡
አቶ ሬድዋን እና አቶ አሰመላሽ በሁለተኛው ክፍለ ጊዜ ባገኙት 20 ደቂቃ በጅምላ ተቃዋሚዎችን በተለይ ሰመያዊና መድረክ ላይ ያደረጉት ውረፋ አቶ አሰፋው ጌታቸውንም ያስቆጣቸው ይመሰላል፡፡ በመጀመሪያ ካቀረቡት የመነሻ ኃሳብ በእጅጉ በተሻለ ሁኔታ የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት የሌለው መሆኑ፣ ኢህአዴግ ርዕዮት ዓለም የሚባል ነገር የሌለው ብቻ ሳይሆን ከኮሚኒዝም እሰከ ነጭ ካፒታሊዝም የሚረግጥ በግለሰቦች ትርጉም የሚመራ ግንባር እንደሆነ አሰቀምጠዋል፡፡ በተለይ ድፍረት አጥተው በግልፅ አይናገሩት እንጂ በተቃዋሚዎች ውስጥ ካለው ክፍፍል በከፋ በኢህአዴግ ውስጥ ያለው የሃሳብ ልዮነት ለከፋ ክፍፍል የሚባቃ እንደሆነ ነገር ግን ስልጣን ላይ በመሆናቸው ግልፅ የሆነ መከፋፈል እንዳላሰዩ ገልፀዋል፡፡ በእኔ እምነት በኢህአዴግ ሰፈር ለመከፋፈል የሚሰጠው ምላሽ በጠብምንጃ የታገዘ እና ወደ ወህኒ የሚያስወረውር እንደሆነ መቀመጥ ነበረበት፡፡ ከዚህ ካመለጡ ደግሞ ሰደት ይሆናል፡፡
ዶክተር መረራ ጉዲና እሰከ ዛሬ ያለቸውን አውቀት ተጠቅመው እንደ ሁልጊዜ በተረጋጋ ሁኔታ በግልፅ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት የሌለ መሆኑ በማሰቀመጥ ከርዕሱ ጋር ተዛማጅ የሆነ ጉዳይ አንስተዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ዶክተር መረራ በእኔ እምነት ከፖለቲካው ግንባር ቢለቁ የምመርጥ ቢሆንም ከቀረቡ ወዲህ ግን አዲስ ነገር ይዘው መመጣት አለባቸው የሚል እምነት አለኝ /ዛሬም የጥብቆ እና የሚኒሊክ አልጋ ምሳሌ ቢቀር እመርጣሁ/፡፡ ኢህአዴግ አብዮታዊም ወይም ዲሞክራሲያዊም ያለመሆኑን ያስረዱበት መንገድ ተመችቶኛል፡፡ ዶክተር መረራ በኢትዮጵያ የሰብዓዊ እና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ጉዳይ ሲነሳ አበክረው ሊያነሱት የሚገባ የነበረ ነገር ግን የዘነጉት ከጎናቸው ተወስደው በእስር የሚማቅቁትን አባላቶቻቸውን ነው፡፡ እነ በቀለ ገርባ፣ ኦልባና ሌሊሳ እና ሌሎች የኦሮሞ ልጆችን በሰም ጠርተው የሚደርሰብቻውን ግፍ ለህዝብ ማሳየት አልቻሉም፡፡ የኦሮሞ ልጆች ከምንጊዜውም በላይ እየደረሰባቸው ያለውን የሰብዓዊ እና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ጥሰት ሊያሳዩን ሙከራ አላደረጉም፡፡ በኢትዮጵያችን በአሁኑ ጊዜ ከኦሮሞ ልጆች እኩል በደል የደረሰበት ያለ አይመስለኝም፡፡ ዶክተር መረራ ለፓርቲዎች ውህደት ጥያቄ ሲቀርብ ኦሮሞነታቸውን የሚያጎሉትን ያህል በሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ጥሰት ብሔረተኝነታቸውን ሊጠቀሙበት አለመቻላቸው ተገቢ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ ለመራጮቻቸው በዚህ ርዕስ ጉዳይ ከዚህ የተሻለ ማሰረጃ ሊሰጥዋቸው የሚችሉበት አጋጣሚ ሊያገኙ የሚችሉ አይመስለኝም፡፡ ለምሳሌ ህገ መንግሰታዊ መብታቸውን ተጠቅመው ሰልፍ የወጡ የአምቦ ዮኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ነዋሪዎች በጥይት የተሰጣቸው መልስ ትክክል ያለመሆኑን ለማስረዳት ከዚህ የተሻለ ጊዜ የሚያገኙ አይመስለኝም፡፡ መብቶችን ለመጠቀም ሁል ጊዜ የሚነሳው ጉዳይ ልክ መሆን አይኖርበትም፡፡
ኢህአዴግ በሁለተኛ ክፍለ ጊዜ ባደረገው ጉንተላ እጅጉን ተበሳጭተው መስመር ከሳቱት በዋነኝነት የሚጠቀሱት ዶክተር መረራ ናቸው፡፡ ተማሪያቸው የነበረው አወያይ ጋዜጠኛ እስኪያቋርጣቸው ድረስ መስመር ጥሰው ሄደዋል፡፡ ርዕሱ “መድበለ ፓርቲ፣ የሰብዓዊና ዲሞክራሲያ መብቶች” ሆኖ እያለ የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ ጉዳዮችን አንሰተው ጊዜያቸውን ጨርሰውታል፡፡ ከውይይት ርዕሱ ጋር የማይሄዱ ነጥቦችን ኢህአዴግ አማራጭ የላቸውም አለን ብለው አድማጭ ሊይዘው በማይችለው ደረጃ ዝርዝሩን ዘርግፈውት በተገቢው ሁኔታ የወከሉትን ግንባር ምልክት እንኳን ሳያስተዋውቁ አጠናቀዋል፡፡ ለሌላ ጊዜ ለክርክር የሚቀርቡ ተከራካሪዎች በወረቀት ላይ የታተመ የምርጫ ምልክት ይዘው መግባት የሚጠቅማቸው ይመስለኛል፡፡
አቶ ይልቃል ጌትነት በአቶ አሰፋው ጌታቸው የክርክር ሂደት በግልፅ በሚታይ መልኩ የደረሰባቸውን መሸማቀቅ በዶክተር መረራ ዘና ያላ አቀራረብ ዱካኩ የተገፈፈላቸው ቢሆንም በቅድመ ክርክር ወቅት የነበረውን ነጥብ አምጥቶ ካለቸው ውድ ጊዜ ለመጠቀም መወሰናቸው እንደ ሁልጊዜውም አጋጣሚውን ለህዝብ ግንኙነት ስራ መጠቀም የፈለጉ ያስመስለዋል፡፡ ክርክሩ ላይ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት የለም ብሎ በግልፅ ያስቀመጡት አቶ ይልቃል የሰብዓዊ መብትን ለማቅረብ የሄዱበት መስመር ሰብዓዊና ዲሞክራሲያ መብቶችን  ለህዝብ በሚገባው ግልፅ ምሳሌ ከማቅረብ ይልቅ ሰብዓዊና ዲሞክራሲያው መብቶችን በመቀላቀል ማቅረባቸው የዝግጅት እጥረት እንደነበረባቸው ለመረዳት አያስቸግርም፡፡ በሰው ፊት ለንግግር ሰንቀርብ ሀምሳ ከመቶ ዝግጅት መሆኑን አቶ ይልቃል የዘነጉት ይመስላል፡፡ ከዝግጅት አንፃር ተዝረክርከው ማስታወሻውን ወደፊት ወደኋላ ሲገልፁ የነበሩትን አቶ አስፋው ጌታቸውን ማንሳት ሳያስፈልግ ነው፡፡
አቶ ይልቃል በሁለተኛውም ዙር የተሰጣቸውን ጊዜ በአግባቡ ከመጠቀም ይልቅ የተሰጠው ጊዜ አንሰተኛ መሆኑን በሚገልፅ ቅሬታ ጊዜ ሲያባክኑ ነበር፡፡ በሁለተኛው ዙር አቶ ይልቃል ያስቆጠሩት ዋነኛ ነጥብ አቶ አስመላሽ ሰለ ሰመያዊ ፓርቲ ጠቅላላ ጉበዔ አጠራር አሰመልክቶ ያነሱት ነጥብ ነው፡፡ ይህ ነጥብ ኦቶ ይልቃል ከመረጃ እጥረት በሚል እወሰደዋለሁ ቢሉም ይህ የጠቅላላ ጉባዔ ጉዳይ ህወሃት/ኢህአዴግ ከምርጫ ቦርድ ጋር ለሰማያዊ ፓርቲ ከተቀመሙት መርዞች አንዱ እንደሆነ ሁሉም ማወቅ አለበት፡፡ አቶ አስመላሽ የሰማያዊ ፓርቲ ደንብ ጊዜ አግኝተው ሊያነበትም ሆነ ሊያስነብቡ አይችሉም፡፡ አንብበው ፓርቲ ማፍረሻ ቀዳዳ የሚያቀብሉ በምርጫ ቦርድ የተቀመጡ ወኪሎቸ አሉ፡፡ ለዚህ ቅብብል የሚሆን ደግሞ የተዘረጋ ህጋዊ የሚመስል መስመር እንዳለ ሁላችንም እናውቃለን፡፡  ለማነኛውም አቶ ይልቃል የነበረውን ጊዜ በርዕስ ጉዳዩ ላይ ብቻ አተኩረው በምድር ላይ ባለ የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ጥሰት አሰደግፈው መከራከር አልቻሉም፡፡ እንደ ዶክተር መረራ በኢህአደግ ትንኮሳ መበሳጨታቸው ቢታወቅም ለመረጋጋት ያሰዩት ጥረት ጥሩ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ዘመኑን የዋጀ ፓርቲ አይደለም እራሱን የሚያወዳድረው ከንጉሶች ወይመ ከደርግ ጋር ነው፣ መሻሻል የማይፈልግ ፓርቲ ነው፡፡ በሚል ያነሱት ነጥብ በኢትዮጵያ ህዝብ ሊያዝ የሚችል አንኳር ጉዳይ ነው - በምርጫ ካርድ ይሁን በህዝባዊ አመፅ ግልፅ ሆኖ አልተቀመጠም፡፡
የመጨረሻውን እድል ያገኘው የድንኩ “አንድነት” መሪ የሆነው አቶ ትዕግሰቱ አወሉ ነው፡፡ አቶ ትዕግሰቱ ከሌሎቹ በተሻለ የሰብዓዊ መብት ለመርገጥ ገዢው ፓርቲ እየተጠቀመበት ያለውን “የፀረ ሽብር ህግ” አንስቶ ለመሞገት ሞክሮዋል፡፡ በምንም መልኩ ግን አስተያየት ሊሰጥበት ያልቻለው ግን የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ጉዳይ ነው፡፡ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ማለት ምን ማለት እንደሆነ ትዕግሰቱ በትክክል ያውቀዋል፡፡ በኢህአዴግ ኢትዮጵያ ይህች ያገኛትን ቦታ በአባላት ይሁንታ ሳይሆን በተደራጀ ሾኬ እንዳገኛት ስለሚያውቅ መድበለ ፓርቲ ስርዓት የለም ሊል አልደፈረም፤ ቢያንስ በመግቢያው ንግግር፡፡ የሚገርመው ግን አሁንም “አንድነትን” ሲጠራ አፉ ይተሳሰራል፡፡ “እንደ አንድነት ማለትም እንደ እኛ አመለካከት” ሲል ውስጡ ያለው የአንድነት መንፈስ እንዳልሆነ ያሳብቃል፡፡ ትዕግሰቱ የአንድነትን አቋም በሙሉ ልቡ ሊናገር የሚችልበት የሞራል ልዕልና ላይ እንደሌለ በሚያሳብቅበት ሁኔታ ላይ ነው የሚገኘው ብል የተሳሳትኩ አይመስለኝም፡፡
አቶ ትዕግሰቱ አወሉ ስለሚያቀርበው ሃሳብ ያለኝን የግል ንቀት ለመተው እየሞከርኩ ቢሆንም ለመያዝ የሞከርኩት ነጥብ የዲሞክራሲ ተቋማት የይስሙላ መሆናቸውን ገልፆ በተለይ ምርጫ ቦርድን ጠቅሶ መለወጥ እንዳለበት ሲናገር የበላበትን ወጨት ሰባሪ ቢያደርገውም እውነት መናገሩን ግን መካድ አይቻለም፡፡ ኢህአዴግ ህዝቡን አፍንጫህን ላስ የሚል ፓርቲ መሆኑን መግለፁም ትክክል ነው፡፡ በዚህ አስተያየቱ ኢህአዴግ ተጨማሪ እድል ባለማግኘቱ ምን እንደሚከተለው ማወቅ አይቻልም፡፡ ለማነኛውም ጌቶቹን በተለይ ምርጫ ቦርድ ታዛዥነቱን አይቶ በሰጠው ወንበር ሰሙን ጠርቶ መዝለፉ ሽርክናቻው አንድነትን ድንክ እሰከማድረግ ብቻ አስመስሎባቸዋል፡፡
የኢህአዴግ የምላሽ ወቅት ሰለባዎች እንደሚጠበቀውም ሰመያዊና መድረክ ነበሩ፡፡  የፈለገ ጠንካራ ተቃውሞ ቢያቀርቡም “አትፓ እና ድንኩ አንድነት” በኢህአዴግ አፍ ለዘለፋ አይፈለጉም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ድንኮች ምንም በማያመጣ መልኩ ተሰርተዋል ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ አንድነትን ድንክ በማድረግ ሂደት ዋነኛዎቹ ተዋናዮች የነበሩት ሁለቱም የኢህአዴግ ወኪሎች አንድ ጊዜ እንኳን አንድነትን ሳይዘልፉ ይልቁንም ጅምሩ ጥሩ ነው በሚል ማለፋቸው ሰራቸው ማጠናቀቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ የኢህአዴግ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት መገለጫ ተብለው የቀረቡልን ምሳሌዎች ግን ተጨፈኑ ላሞኛችሁ ነገር ነው፡፡ እነርሱም፤
·         አሁን 75 ፓርቲዎች በሀገራችን መኖራቸው የመድበለ ፓርቲ መገለጫ ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞም አሁን ለክርክር የቀረቡት ፓርቲዎች መኖር ዋናኛ ማሳያ ነው፡፡ እንደ ኢህአዴግ በፓርቲ ምዝገባና ቁጥር የመድበለ ፓርቲ ቢለካ እውነት ነበር፡፡ በወረቀት የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዳለ ሳይካድ በተግባር ገን የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲኖር የማይፈቅደው ኢህአዴግ ጉንጭ አልፋ ክርክር ያቀርባል፡፡ እምነታቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ኪራይ ሰብሳቢዎች ናቸው ብለው እንዲጠፉ እየሰሩ ለእርዳታ ሰጪዎች ፍጆታ የፓርቲነት ሰርተፊኬት በማደል የመድበለ ፓርቲ ስርዓት አለ ብለን እንድናምን ይፈልጋሉ፡፡ በአሜሪካን ሀገር በዋነኝነት ሁለት ፓርቲዎች መኖራቸው ዲሞክራሲ ያለመኖሩ ማሳያ ነው እንደማለት ነው፡፡ የኢህአዴግ ጉንጭ አልፋ ክርክር፡፡
·         ለምርጫ ውድድ የቀረቡ ዕጩዎች ሌላኛው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ማሳያ አድርገው ኢህአዴጎች አቅርበዋል፡፡ ማንም እድሉን ሊሞክር ለምርጫ ዕጩ ሆኖ እራሱን ማቅረብ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ማሳያ እንዴት ሊታይ እንደሚችል አቶ አሰመላሽ እና አቶ ሬድዋን ብቻ ናቸው የሚያውቁት፡፡ ይህ በቅርቡ የመጣ የመድበለ ፓርቲ ስኬት መገለጫ ነው፡፡
·         ለምርጫ ማስፈፀሚያ የተመደበው በጀት ደግሞ ሌላው የመድበለ ስርዓት ስለመኖሩ ማሳያ ተድረጎ ነው የተብራራልን፡፡ አስገራሚው ነገር ከተመደበው ገንዘብ አብዛኛውን የሚወሰደው ገዢው ፓርቲ መሆኑ እየታወቀ፤ ፓርቲዎች በምርጫ ሰሞን በሚያገኙት በዚህ ገንዘብ የመድበለ ፓርቲ ስርዓትን ለማጠናከር ምን ሊያደርጉበት እንደሚችሉ ማሰረዳት አይችሉም፡፡ ተመደበ የተባለው ገንዘብ ዋነኛው ወጪ ከ45 ሺ በላይ ለሚሆኑ ምርጫ አስፈፃሚዎች አበል ሲሆን፤ ለአንድ ዕጩ ተወዳዳሪ ብር 500 በማይደርሰበት ሁኔታ ይህ ገንዘብ እንዴት እንደሚጠቅም ኢህዴጎች ሊያስረዱን አይችሉም፡፡
·         በጣም ያስገረመኝ አንዱ መከራከሪያ “የመድበለ ፓርቲ በሊብራል ዲሞክራሲ በሚያራምዱ ሀገሮች ለብሔር ብሔረሰቦች የማይፈቅድ ነው” የሚልው ነው፡፡ ኢትዮጵያን የተለየች የብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ አድርጎ ለማሳየት የሚደረገው የተሳሳተ ነገር አሁንም ቅጥ ያጣ ይመስላል፡፡ በዓለም ላይ አሉ የሚባሉ ብሔሮችና ብሔረሰቦች በሙሉ የሚኖሩባት ሀገር አሜሪካ ውስጥ በፈለጉት ቡድን ለመደረጃት አንድም ጥያቄ እንደማይቀርብ የምናውቅ አይመስላቸውም፡፡ ሊብራል ዲሞክራሲን ያለ ስሙ ሰም እየሰጡ የራሳቸውን የፖለቲካ መስመር አንዴ አብዮታዊ ሌላ ጊዜ ልማታዊ ዲሞክራሲ እያሉ ሊያደናብሩን ይፈልጋሉ፡፡ ይህ የብሔርና ብሔረሰብ ፖለቲካ ጉዳይ ሲነገር የሚያስታውሰን አንድ ነገር “ለምለሚቱ ሀገሬ” የሚለው ነገር ነው፡፡ በሌሎች ሀገራት ሳር የማይበቅል፣ ወተት ማር የማይገኝበት፣ ወዘተ ይመስለን የነበረው ዓይነት አሳሳች ምሳሌ ነው፡፡

በመጨረሻም በክርክሩ የነበሩ ተቃዋሚ እና “ተቃዋሚ ተብዬ” ፓርቲዎች በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባት ውይይት ሲደረግ በቅርብ ርቀት በአንድነት ላይ የተፈፀመውን የመንግስታና ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባት ለማጠናከር መቆም ያለበትን ምርጫ ቦርድ ሴራ በምሳሌ አንስተው ለመሞገት ያለመሞከራቸው፤ በተለይ መድረክና ሰማያዊ ፓርቲ የአንድነት ድንክ መሆን እነሱን ከፍ ማድረጉን በግልፅም ባይሆን በውስጣቸው የፈጠረላቸውን ደስታ የሚያሳይ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ አንድነትን ድንክ በማድረጉ ብቻውን እንዳልተጠቀመም ማሳያ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ የሚችለውን በመምረጥ አንፃር በጣም ተሳክቶለታል፡፡ በዚህ ፅሁፍ ለአንድነት ፓርቲ አመራሮች እግረ መንገዴን የማስታውሳቸው ዘወትር በነበሩን ስብሰባዎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማስተባበር ስንደክም ከእኛ ይቅር ስንል የነበረው ለእነዚህ ፓርቲዎች መሆኑን ማስታወስ ይኖርብኛል፡፡ በተለይ ሰማያዊ ፓርቲን አስመልክቶ አንድነት ፓርቲ ውስጥ የነበረንን ልበ ሰፊነት ሳስበው በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ለምን አደረግነው የሚል ቁጭት የለብኝም፡፡
አንድነት ፓርቲ በዚህ ክርክር ውስጥ ቢኖር ኖሮ በመጀመሪያ ከኢህአዴግ እኩል ሁሉንም ለመከራከር እድል ነበረው ፓርቲ ይሆን ነበር፡፡ ምክንያቱም 450 ዕጩዎች ለፌዴራል ምክር ቤት እና 1200 የማያንሱ የክልል ምክር ቤት ዕጮዎች ስለሚያቀርብ፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ለመከራከር ሊመጡ የሚችሉትን ትንታግ የአንድነት ወጣቶች ሳሰብ እንባ እየተናነቀኝ ነው፡፡ የዛሬ አምሰት ዓመት የዚህን ተመሳሳይ ክርክር አንድነትን ወክሎ  የተከራከረው ምን አልባትም በዚህ ክርክር መነሻ ቂም ተይዞበት የነበረው፣ ዛሬ በወህኒ የሚገኘው አንዱዓለም አራጌ ነው፡፡ አንድነት ፓርቲ ክርክሩ ከመደረጉ በፊት በዚህ ጉዳይ ላይ በሚኖረው 6 ደቂቃ የመነሻ ኃሳብ ልናነሳ የምንችለውን ቢያንስ 12 ነጥብ ይዘን እንገባ ነበር፡፡ ወይም 10 ነጥብ እና በቀሪው ሁለት ደቂቃ ለህዝብ ውይይት ሊጭር የሚችል ሃሳብ የሚነሳበት ይሆን ነበር፡፡ ሁለተኛው ዙር ዘጠኝ ደቂቃ በዝርዝር ህገ መንግሰታዊ ድንጋጌዎችን አሰመልክቶ ኢህዴግ የሚሰራቸውን የክርክር ፋውሎች ለህዝብ የምናጋልጥበት ይሆን ነበር፡፡ ለዚህ ነው በ2007 ኢህአዴግ የሚችለውን መርጦዋል የምንለው፡፡
ለማጠቃለል ተቃዋሚዎች በኢህአዴግ ትንኮሳ ተገፍተው በመድበለ ፓርቲ እና በሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ዙሪያ ትኩረት ሰጥተው ለመከራከር አልቻሉም፡፡ ክርክሩን በኢህአዴግ ሜዳ ላይ ለማድረግ ማተኮር የነበረባቸው “ህገ መንግሰት” ላይ የተዘረዘሩትን መብቶች እያነበቡ በተግባር የገጠመውን ፈተና በማቅረብ ህዝቡ እነዚህን ጉዳዮች ገዢው ፓርቲ የአፈፃፀም ችግር ናቸው ቢልም በመርዕ የማያምንባቸው መሆኑን እራሱ ኢህአዴግ ከፃፋቸው የፖሊሲ፣ሰትራቴጂና የርዕዮታለም ትንተና መፅሃፉች ጋር እያጣቀሱ ማስረዳት ነበረባቸው፡፡ የህገ መንግሰቱ ምዕራፍ ሶሰት ክፍል አንድ ከአንቀፅ 14 -28 የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎችን በማየት በተግባር የገጠሙትን ፈተናዎች፤ ምዕራፍ ሶሰት ክፍል ሁለት ከአንቀፅ 29-44 ዲሞክራሲያዊ መብቶቸን በማየት የገጠሙትን ፈተናዎች በዝርዝር መተንተን ይቻል ነበር፡፡ በዚህ መስመር ክርክሩ ቢደረግ ኢህአዴግ ሊከራከር የሚችለው ህገመንግሰቱን ለማዘጋጀት ህይወትና ደም ተከፍሎበታል ከሚል ፉከራ ውጭ ለምን በተግባር ላይ እንደማያውላቸው ሊያስረዳ አይችልም ነበር፡፡ ምንም በቂ ምክንያት ሊኖር አይችልም የሚል እምነት አለኝ፡፡
ቸር ይግጠመን!!!!


No comments:

Post a Comment